ብዙ አንገብጋቢ የሆኑ ወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች አሉ፡፡ የቱን ጥለን የቱን እንደምናነሳ ራሱ ይቸገራል፡፡ ወዲህ ስንል በፖለቲካው መድረክ የዴሞክራሲው አፈናና እመቃ ገዝፎ ይታያል ብቻ ሳይሆን የማፊያው ሥርዓት - አልባ የወያኔ ሥርዓት መፈናፈኛ አሳጥቶን ይገኛል፡፡ ወዲያ ስንል የኑሮ ውድነቱ ከጥቂት ዘመነኞችና አጭበርባሪ ተውሳኮች በስተቀር አብዛኞቻችንን በቁማችን ገድሎ ቀብሮናል፡፡ እንዲያ ወዲያ ስንል ደግሞ በቂ የእህል ምርት ያለመኖር፣ ሥራ አጥነት እንዲሁም በዬጊዜው በአስደንጋጭ ሁኔታ እየጨመረ በሚሄድ የሕዝብ ብዛት ምክንያት እየተባባሰ የመጣው የምግብ ዕጥረት እያስከተለው ያለው ርሀብ በቀላል ሊድኑ ከሚችሉ በሽታዎች ሳይቀር እየተባበረ ሕዝብን እየፈጀ ነው፡፡ በጥቅሉ እንደ አንድ ማኅበረሰብ በመኖርና ባለመኖር አስቸጋሪ ምርጫዎች ውስጥ ተቀርቅረን የአንድዬን መልስ ብቻ እየተጠባበቅን እንገኛለን፡፡ ከሁሉም በባሰ ደግሞ በሃይማኖት ሰበብ የገባብን ችግር የተግዳሮቶቻችንን ጡዘት በብዙ እርከን ከፍ አድርጎት ባልጠፋ ችግር አላስፈላጊ መሰናክል እየፈጠርን አንዳችን አንዳችንን የጎሪጥ በማየት ‹ነገ ደግሞ ምን ይፈጠር ይሆን?› በሚል ሥጋት ተወጥረን እንደነገሩ ይመሻል ይነጋል፡፡ በመሀሉ ግን ለዚህ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ውጥንቅጡ የወጣ ቀውስ የዳረጉን የውስጥ ምንደኞችና የውጪ ጌቶቻቸው በኛ የማያባራ ሥቃይ እየተዝናኑ ለነሱ የተመደበው መከራ እስኪደርስ ለጊዜው በሰው ደምና ወዝ በተፈጠረ ሀብት በመዘፈቅ በፈንጠዝያና በደስታ ይኖራሉ፡፡
ጆሮ የማይሰማው የለም፡፡ በቀደምለት የ97ን የወያኔ ዳግማዊ ቀይ ሽብር ለማጣራት በወያኔው መንግሥት ተቋቁሞ በነበረው ኮሚሽን ከነበሩት 10 አባላት የሁለቱን አቋምና የመንግሥት ወገንተኝነት በኢሣት ቴሌቪዥን ተከታተልኩ፡፡ እነዚህ የታሪክ ጉድፎች ‹ሼህ› ኤሊያስና ‹ዶክተር› መኮንን ዲልጋሳ የሚባሉት ናቸው፡፡ የነዚህ ‹ሰዎች› የሃሳብ ልዩነት መሠረት መንግሥት በወቅቱ ሕገ መንግሥቱን ከ‹ጎዳና ነውጠኞች› ለመከላከል ባደረገው ጥረት የተጠቀመው ኃይል በእጅጉ ተመጣጣኝ እንደሆነና እንዲያውም እንደሼካው ከሆነ ተቃዋሚዎች በ16 ሺህ ሰው መስዋዕትነት መንግሥትን እንገለብጣለን በማለታቸውና የሞተው ሰው ቁጥር አንድ ሺህ እንኳን ባለመሙላቱ ከተመጣጣኝም በታች መሆኑን ገልጸዋል - እንደሳቸው እሳቤ መንግሥት ዜጎችን በመጨፍጨፍ ረገድ ገና ሊያወራርደው የሚገባው ከ97ዓ.ም የሚወራረስ ቀሪ ሒሳብ አለው የሚሉ ይመስላል፡፡ እነዚህ ‹ሰዎች› እንደሰውም እንደሀገር ዜግነትም እንደመሬታዊ ነዋሪነትም በጣም ያሳፍራሉ፡፡ በጊዜው እዚህችው ሀገር ውስጥ አብረን ስለነበርን ያን የመሰለ የተቃዋሚዎች የ10 እና 16 ሺህ ሰው የደም ግብር እሳቤ ሼካው ከየት እንዳገኙት አላወቅሁም፤ በወቅቱም ይህን መሰል ነገር ከማንም አልሰማሁም፡፡ ይህን መሰል ነገር ቢናገሩ ልሰማ እችል እንደነበር እገምታለሁ፡፡ ግን ሼሁ የአላህ ሰው ሳይሆኑ በግድያና በጭፍጨፋ የሚደሰተውና ካለነዚህም የማይኖረው የሸይጣን ልዑክ ስለሚመስሉኝ ከወያኔው በልጠው ወያኔን ሆነው ማየታችን ብዙም ሊያስደንቅን አይችልም፡፡ በዚያ ላይ እንደሰማሁት የዘር ጉዳይም እየሳባቸው ሃይማኖታቸውን ያስከዳቸው መስሎኛል፡፡ እንጂ እርግጠኛ ነኝ በእስልምና ሃይማኖት ውስጥ መብቱን የጠየቀን ዜጋ እንደዐይጥ ጨፍጭፍ የሚል ጥቅስ አይኖርም፡፡
በዚያ ኮሚሽን ውስጥ ሰብሳቢውን አቶ ፍሬሕይወትን ጨምሮ ስምንቱ ዕንቁ ዜጎች እውነትን አከበሯት፤ ለሥጋቸው ሳይሳሱ ለማተባቸው አድረውና ለወጡበት ሕዝብ ወግነው ነፍሳቸውን በፈጣሪ ዘንድ ትልቁን ቦታ አስሰጡ፡፡ ኤሊያስ የተባሉት ለሥጋቸው ያደሉ ሃይማኖተኛ ነኝ የሚሉ ሰው ግን በሰው ሃይማኖት እያላገጡ ቀላልነታቸውንና ግብዝነታቸውን በኩራት አጋለጡ፤ እንደዚያ በትዕቢት እየተወጣጠሩ የሰውን ሃይማኖት ለማሽሟጠጥ መሞከሩ ግን አለማወቅን እንጂ ብልህነትን አያመለክትም፡፡ ደግሞም በዘወርዋራም ይሁን በቀጥታ መንገድ ኢየሱስ(ዒሣ) ላይ የማሸሞር የሞራል ብቃት ያላቸው አይመስለኝም፡፡ ከእዳሪ በማያልፍ አንድ እንጀራና ከመሬት በማያልፍ የዘረኝነት ልክፍት የተሸነፉት የዚህ ሰው ስም በታሪክ ዐምድ በጥቁር ቀለም ተጻፈ፡፡ ያሳዝናል፡፡ “በኔ ሃይማኖት ‹ግራህን ሲመቱህ ቀኝህን አዙርለት› የሚል ነገር የለም፡፡ በዚህ እኔ አላምንም…” እያሉ ሰይጣናዊ ጥቅሳቸውን ሲደረድሩ እኔ አዘውትሬ በምከታተለው የእስላማዊ ‘Peace TV’ በስብከቱ ከልብ የምወደው የዶክተር ናይክ ዛኪር ሃይማኖታዊ የመቻቻል ስብከትና አስተምህሮ በአእምሮየ ብልጭ አለብኝ፡፡ እኙህ ሰው ከጀሃነም እንጂ ከእስላማዊ ልሂቃን መንደር እንዳልመጡም ወዲያውኑ አመንኩ፡፡ አንድ የሃይማኖት አባት እንዲህ ያለ ንግግር በፍጹም አይናገርም - ሼህ ኤሊያስንና እሳቸውን መሰል የነፍስንና የሥጋን መንገድ ለይቶ የማያውቅ ካልሆነ በስተቀር፡፡ የኢጣሊያንን የቅኝ ገዢ ወታደር ባርከውና ቀድሰው ወደኢትዮጵያ የላኩት የሮማው (ሊቀ?) ጳጳስ ትዝ አሉኝ፡፡ በየሃይማኖቱ እኚህን መሰል ማፈሪያ ሰዎች መኖራቸውን ሳስብ በሃይማኖት ካባ ውስጥ የሚሠራው ወንጀልና ደባ ቁልጭ ብሎ ታየኝ፡፡ ምን ይሻለን ይሆን? ለጊዜው እኔ እንጃ!እያደር ግን ሁሉም እየጠራ ይሄድና እያንዳንዳችን የየመክሊታችንን እንደምናገኝ ጥርጥር የለውም፡ ፡
በኢትዮጵያ እንደሚታየው ያለ የሃይማኖቶች በተለይም የክርስትናና እስልምና እምነት ተከታዮች ተሳስቦና ተፈቃቅዶ መኖር የትም የለም ቢባል ማጋነን አይደለም፡፡ በዚህን የመሰለ የጋራ ኅላዌ ላይ ይህን የኤሊያስን የመሰለ ቆርፋዳ ንግግር መቸለስ ምን ዓይነት ቅሬታን ሊፈጥር እንደሚችል መገመት አይከብድም፡፡ ለራሳቸው የማያውቁ ገልቱ ግለሰብ ሆነው ሳሉ በፍቅርና በመተሳሰብ በሚኖሩ የሃይማኖት ተቋማት ላይ ሊዘሩት የተነሱትው ወያኔያዊ የጠብ ዘር ግን ሊታረም ይገባዋልና ሌሎቻችን ከኚህ በቁም የሞቱ ሰው ንግግር ተነስተን ልንማር የሚቻለንን ቁም ነገር እንማር፡፡ መማር ደግሞዕድሜም ሆነ የሃይማኖት ድንበር አይገድቡትም፡፡
ከስሙ ብንነሳ የተማሩቱ እንደሚነግሩን እስላም ማለት ሰላም ማለት ነው፡፡ ሰላም ማለት ደግሞ ለፍቅር ሲባል ሁለት ወገኖች ልዩነቶቻቸውን በመተው መሀል ድረስ በመምጣት የሚተቃቀፉበት እንጂ አንደኛው አንድ ጠርዝ ላይ ቆሞ ሌላኛው መጥቶ እንዲያቅፈው የሚጠብቅበት የትምክህት ዐውድ አይደለም፡፡ የሚሰበከውና በተግባር የሚገለጠው እስካልተለያየ ድረስ በእስልምናም ሆነ በክርስትና ተቻችሎ መኖር ዋነኛው የሕይወት ምሰሶ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ ነብዩ መሀመድ(ሰ.ዐ.ወ) በሀገራቸው ተከታዮቻቸው ሲገደሉና ሲሰቃዩ፣ ሰውን አክባሪ እንግዳን ተቀባይ የክርስቲያኖች ንጉሥ የሆነ በኢትዮጵያ መኖሩን ገልጸው ወደዚያች ሀገር እንዲሄዱ፣ ካልነኳቸውም እንዳይነኳቸው በጥብቅ አስጠንቅቀው ነበር ወደዚች ቅድስት ሀገር እንዲሰደዱ የመከሯቸው፡፡ ይሄ በታሪክ ተመዝግቦ ያለ ነገር ነው፡፡ ዛሬ ዓለም ዘወርዋራ ናትና አሁን በምንገኝበት ውሉ የጠፋበት አስቸጋሪ ሁኔታ ላይ ብንሆንም የጥንቱ ሊረሳ አይገባም፡፡ የሀገራችን መመሪያ ደግሞ ‹ሀገር የጋራ ሃይማኖት የግል› በመሆኑ የፈለጉትን ሃይማኖት እየተከተሉ መኖር ያልተከለከለ ብቻ ሳይሆን የተፈቀደም መብት ስለሆነ ከዚያ ማፈንገጥ ተገቢ አይደለም፡፡ የሌለ ችግርን እየፈጠሩ በሃይማኖት ሰበብ ምድርን ጦር አምጪ ማለት ደግሞ አይገባም፤ ፈጣሪም የለመኑትን የማይነሣ የነገሩትንም የማይረሣ ነውና ይህ ዓይነቱ ቅብጠት ቢቀርብን የተሻለ ነው፡፡ ዘመናችን የ21ኛ መቶ ክፍለ ዘመን የዕውቀትና የቴክኖሎጂ ምጥቀት እየተመዘገበበት ያለ እንጂ የመካከለኛው መቶ ክፍለ ዘመን የክሩሴድና የጂሃድ ዘመነ ድንቁርና ባለመሆኑ ሁላችን በፍቅርና በውዴታ ተስማምተን መኖሩ ነው የሚያዋጣን፡፡ የፉክክር ደጃፍ ሊኖር አይገባም - ሳይዘጋ ማደሩ ለሁላችን ስለማይበጅ፤ ተባብረን በሮችንና ብርድ ወይም ንፋስ የሚገባባቸው ቀዳዳዎችን ሁላችን እየተሸቀዳደምን በፍቅር ስለፍቅር መዝጋት ይኖርብናል፡፡ እልህና ባለፈ ታሪክ ላይ የተመሠረተ ብቀላና የቂም ቋጠሮ ደግሞ አንዱን ወገን ብቻ ሳይሆን ሁሉንም ይጎዳል፡፡ ያላጠፋን ወገን መበቀልሞ ላም ባልዋለበት ዓይነት ስለሆነ ከጅምሩ ሊታሰብም አይገባም፡፡ የየትኛውም ጠርዝ የለቀቀ አመለካከት ሰለባዎች ብንሆን ተጎጂዎቹ እኛና ቀጣዩ ትውልዳችን ብቻ
ነን፡፡
በአማርኛ አንድ ጥሩ አባባል አለ፡፡ “ያንቺ ልጅ የኔን ልጅ መትቶት ከሆነ ምች ይምታው፤ የኔ ልጅ ያንቺን ልጅ መትቶት ከሆነ ግን መቼም” አለች አሉ አንዷ ፍርደ ገምድል፡፡ ማሰብ ያለብን “እኔስ ብሆን? ይሄ ነገር ለኔስ ቢመጣ?...” ብለን ነው፡፡ የኅሊና ፍርድና እውነት ደግሞ ጉልበት ሲሰማን የሚጨቆኑ፣ ገንዘብ ስናገኝ የሚታፈኑ፣ ሥልጣን ሲኖር የሚደፈጠጡ፣ የሰው ምልዓት ሲታይ የሚረሱ ሊሆኑ አይገባም፤ የእውነት አምላክ ስላለ ሁሉን ያያልና፡፡
በግልጽ እንነጋገር፡፡ መሸፋፈን ይቅር፡፡ ሁሉም በጊዜው ይገለጣልና ሃቅን ተመርኩዘን ከአንጀት መነጋገሩ ቅሬታን ለማስወገድ የመጀመሪያ እርምጃ ነው፡፡ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያን በአንደኛው አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን አንድ ሙስሊም ወይም አንድ የፕሮቴስታንት የክርስትና እምነት ተከታይ ገብቶ ካህናትና ምዕመናን በሚመስጥ የስብከት አገልግሎት ላይ እያሉ ይህ ሰው ‹ማርያም እንትን ነበረች! እንኳን ልታማልድ ለራሷም አልዳነችም! ከአላህ በቀር እግዚሃር የሚባል የለም! ሁላችሁም …› ቢሉ - በርግጠኝነት ነው የምነግራችሁ - ይህን መሰሉ ሰው እንዳበደ ተቆጥሮ ይታዘንለታል ይጸለይለታልም እንጂ ማንም ዝንቡን እሽ አይለውም፡፡ ምዕመናን በከዘራ ቀሳውስት በመቋሚያ ጨፍጭፈው ይገድሉታል የምትሉ ካላችሁ ተሳስታችኋል፤ ቢያንስ በዚህ ዘመን እንዲህ ያለ ሞኝነት የለም፡፡ የዚህ ዓይነት አጋጣሚዎችን እኔ ራሴ በተገኘሁባቸው የአምልኮት ጊዜዎች ስለታዘብኩ ሰው ከንፈሩን እየመጠጠ ሲያዝን እንጂ ‹ምናባቱንና ይሄን እንትን ደብድበህ አባርልኝ፤ ወደዚያ አንገቱን ቀንጥስና ገላግልልኝ!› የሚል አንድም ሰው አላየሁም፡፡ ባይሆን ድምጹ የሚረብሽና ፕሮግራምን የሚያሰናክል ከሆነ ዘበኞች ተጠርተው ገፋፍተው እንዲያስወጡት ይደረጋል፡፡
ይህ ለምን ሆነ ስንል አንደኛ ምዕመናን በፈጣሪ ፍርድ መግባት እንደሌለባቸውና መቅጣትም መግደልም ማዳንም መኮነንም የእግዚአብሄር ተግባራት እንደሆኑ ይረዳሉ፤ ሁለተኛ የመጻሕፍት አስተምህሮ ሼህ ኤሊያስ ያላገጡበት ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚያስተምረን ጠላትህን ውደድ፣ ክፉን በክፉ አትቃወም፣ አትግደል፣መጎናጸፊያህን ቢጠይቅ እጀ ጠባብህን ጨምርለት… ስለሚሉ በነዚህ ተገቢ ሕግጋት አማካይነት ሕዝቡ በፈጣሪ ሥራ እንዳይገባ የለዘበ ስብዕናን ተላብሶኣል፤ ሦስተኛ የመንግሥትን ሕግ ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ ያም ሕግ ተጠርጣሪ ወንጀለኛንና ጥፋተኛን ይዞ ወደ ሕግ ማቅረብ እንጅ በኦሪታዊ የሀሙራቢ ‹ዐይንን ለዐይን›ና ‹ጥርስን ለጥርስ› ወይም እንደዘመነ ጻፎችና ፈሪሣውያን የ‹ስቅሎ፣ ስቅሎ› የወል ሥርዓተ አልበኝነት አንድ ሰው እንደዐይጥ አይጨፈጭፍም፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ኋላ ቀር ፍርድ እጅግ አደገኛና ኃላፊነት የሚወስድን ሰው ደብዛ የሚያጠፋ ከትክክለኛ ስብዕናም የማይመነጭ ደመ ቁጡነት ነው፡፡
እዚህ ላይ አንድ የቆዬ ታሪክ እንይ፡፡ በጥንት ዘመን በግሪክ ሀገር ሁለት ሴና የሚባሉ ታዋቂ ሰዎች ነበሩ፡፡ አንዱ ፈላስፋና ባለቅኔ ነው፡፡ ሌላው የፖለቲካ አማካሪ ነው፡፡
የፖለቲካ አማካሪው ጥፋት አጠፋ ይባልና ሕዝቡ ሊገድለው በስሙ አማካይነት ሲያፈላልግ ያኛውን ሲና ይይዙታል፡፡ ‹እንዴ! እኔ እኮ ባለቅኔው ሴና ነኝ!› ቢላቸው ‹ግዴለም፣ ሴና በመሆንህ ብቻ እንገድልሃለን!› ብለው ያለጥፋቱ በስሙ ብቻ ገደሉት ይባላል፡፡ ይህ እንግዲህ ማኅበረሰብኣዊ ዕብደት ካልሆነ ሌላ ስም ሊሰጠው አይችልም፡፡ የ‹ሞብ› አደገኛነት እዚህ ላይ ነው፡፡ ‹ሞብ› ደግሞ ያው ‹ሞብ› ነው - ከሳሽ ተከሳሽ - ዳኛ ጠበቃ ሕግ ፍርድ ቤት … የሌለው እጅግ አደገኛ የሀገርና የኅብረተሰብ ጠንቅ ነው፡፡ ይህን መሰሉን ነቀርሣ የሚጠቀሙበት ተንኮለኞችና ሥውር የጥፋት ተልዕኮ የሚያራምዱ ወገኖች ናቸው፡፡ በዚህ ረገድ የሚታየውን አደጋ ለመቀነስና በሂደትም ለማጥፋት ታዲያ ከየሃይማኖት ተቋማቱና ከምሁራን አካባቢ ራሳቸው ቀድመው የነቁ አብቂዎች ያስፈልጉናል - ዐይንን ገላጭ አንቂዎች፡፡ በሀገራችንም ሆነ በመላው ዓለም ይህን መሰሎች የዕብደት ምልክቶች ሞልተዋል፡፡ በጅምላ መፍረድ፣ በጅምላ ሆ እያሉ ንጹሓንን መፍጀት፣ በቅድመ አእምሮ ፍርድ በጥላቻ በመሞላት በአንዱ ወገን ላይ መዝመት፣በሃይማኖትና በዘር በቋንቋ ሰበብ ወገንን ማግለል፣… እነዚህ ሁሉ ከእውነተኛው የፈጣሪ መንገድ የወጡ ናቸው፡፡
ከፍ ሲል በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ቢገኙ ብዬ እንደጠቆምኩት ዓይነት ከጤናማ አካሄድ የወጣ አሠራር በመስጊድ ውስጥ ቢገኝስ ብለን እንጠይቅ፡፡ የምናገኘው ምስል አያስደስተንም፡፡ መናገሩም ይቅርብኝ፡፡ ይሁንና በሀገራችን ይህን መሰሉ አዝማሚያ እስከቅርብ ጊዜ ድረስ አይስተዋልም ነበር፡፡መቻቻልና በኔ ይቅር ባንተ ይቅር ነግሦ ይታይ ነበር፤ አንዱ የአምልኮ ቤት ሲሠራ ሌላኛው ይረዳው ነበር፡፡ በሩቅ የምንሰማውና የምንታዘበው ክስተት ወደ ሀገራችን እንዳይገባና ሥር እንዳይሰድ ተባብረን ከአሁኑ እናጨንግፈው፡፡ ነገሩ ያደረች ባቄላ ከመሆኑ በፊት ወደቀድሞው ለዘብተኛ አቋማችን እንመለስና ቆም ብለን እንተያይ፡፡ ሌላው ሁሉ ቀርቶ በየትም የሌለ የምግብ ልዩነት ያለው እንኳን እኛ ሀገር ውስጥ ነው፡፡ ይህም ልዩነት የተተከለው ባለማወቅ እንጂ በማወቅ አይመስለኝም - ለነገሩ ያ ብዙም አልለያየንም፡፡
በእምነት ብቻ ሳይሆን በአኗኗርም ብዙ የባህልና የትውፊት መስተጋብሮች ያሉን ሕዝብ ስለሆንን ከፍ ሲል በድርበቡ የገለጥኩትን የመሰለ ከውጪ የመጣ ተፅዕኖ አያዋጣንም ብዬ በሙሉ ልብ ልናገር እወዳለሁ፡፡ የሚያዋጣን እንደስከዛሬው አንዱ ሲያጠፋ ሌላው እየገሰጸና እየመከረ ተግባብቶና ተነፋፍቆ መኖሩ ብቻ ነው፡፡ ይህን የምለው ብዙ ነገር በአእምሮዬ እየተመላለሰ ስለሚያስጨንቀኝ ነው፡፤ የአንዳንድ መጤ አክራሪዎች አካሄድ አላማረኝም፡፡ እነዚህ አክራሪዎች ደግሞ ሳይናገሩ ያስታውቃሉ፡፡ ኢትዮጵያዊውን እስላምና አክራሪውን እስላም በዐይነ ውኃቸው መለየት እንችላለን፡፡ አክራሪው ከፈሱ ጋር የተጣላ ነው፡፡ ከርሱ ጋር ለአንድ ደቂቃ እንኳን መነጋገር አይቻልም፤ የሚቀናው በኪሱ የወተፋትን ጩቤ አውጥቶ ‹አላሁዋክበር!› ማለትና ሬሣን አጋድሞ መፎከር ነው፡፡ ይህን መሰሉን አውሬነት በአልቃኢዳ የዩቲዩብ ዘግናኝ ምስል ስለተመለከትኩ ከዚህ ዓይነቱ ዐረመኔ ተግባር ሀገራችንን እንዲጠብቅ በበኩሌ በገራገሮቹ የእስላምና የክርስቲያን የጥንቶቹ አባቶችና እናቶች ስም አምላክን እለምነዋለሁ፤ እናንተም የበኩላችሁን ጸልዩ፡፡
ብዙዎቻችን ወያኔ የሚለውን ሁሉ ላለማመን ቃል አለብን፡፡ የእረኛው ቢጤ እንዳይሆን ግን እሰጋለሁ፡፡ ለዚያ ደግሞ ማስተማመኛ በተለይ ከልሂቃን ሙስሊሞች ብዙ
እንጠብቃለን፡፡ እረኛው በጎቹን ቀበሮ እንደበላበት እያስመሰለ ሲጮህና ሰዎቹ እንዲደርሱለት በውሸት ሲያታልል ቆይቶ በመጨረሻው የምር ቀበሮዎች መጥተው ዘነጣጥለውለት ሲሄዱ ቢጮህ አንድም የሚመጣለት ሰው አጣ፡፡ እኛም እንደዚያ እንዳንሆን እፈራለሁ፡፡ ለዚህ መድሓኒቱ ርስ በርስ እንድንፈራራ ያደረገንን ብልሹ የወያኔ ሥርዓት በጋራ አስወግደን የጋራ መተማመን የሚፈጠርበትና አንዱ በሌላው ላይ ሸክም የማይጭንበትን ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የመሠረትን እንደሆነ ነው፡፡
ኤሎሄ እንበል፡፡ “የኢትዮጵያ አምላክ ሆይ ጸሎታችንን ስማ፣ በመከራችን ቀን ፊትህን ከኛ አትመልስ፡፡” ይህን ደግሞ ልብ እንበል! ሳዑዲ ኢትዮጵያ ውስጥ ከገባች ወዮ ለኛ! ኢራን ኢትዮጵያ ውስጥ ከገባች ወዮ ለኛ! ሦርያ ኢትዮጵያ ውስጥ ከገባች ወዮ ለኛ! አፍጋኒስታን ኢትዮጵያ ውስጥ ከገባች ወዮ ለኛ! ፓኪስታን ኢትዮጵያ ውስጥ ከገባች ወዮ ለኛ! አልሻባብና አልቃኢዳ አል ምናምን ሁላ ተጠራርታ ኢትዮጵያ ውስጥ ከገባች ወዮ ለኛ! “ስለዚህ” እንበልና ጸሎታችንን እንቋጭ - “ስለዚህ፣ አምላክ ሆይ ለጥፋት ያቆበቆቡ ፀረ - ኢትዮጵያ ኃይሎችን አስታግስልን፤ እስካሁን በደርግና በወያኔ ያየነው አበሳ ከበቂ በላይ ነውና ከአሁን በኋላ ምሕረትህን ላክልን፤ አሜን፡፡”
እስላምም ክርስቲያንም ሰላማዊ ሕይወትን ይፈልጋሉ፤ አፈንጋጮችና በአክራሪነት የተሠለፉ ጥቂቶች ብቻ ናቸው በዕልቂትና በመሠያየፍ የሚያምኑ - ደግሞም እነሱ አይደሉም እየሞቱ ያሉት፤ ለዕኩይ ዓላማቸው የሚሞቱላቸውን ንጹሓን ዜጎች ከየሀገሩ እየለቀሙ ያዘጋጃሉ እንጂ እነሱ በምቹ ሥፍራ ተቀምጠው ነው በገንዘባቸው የሚፈልጉትን ሁከት የሚፈጥሩት፡፡ እነሱን የማያውቅ ማን አለ? አንዷ ሀበሻ ከአንገቷ በስህተት የወጣን የወርቅ መስቀል በጣጥሶ መሬት ላይ በመጣል የሚረጋግጥ መንግሥታዊና ሕገ መንግሥታዊ ድጋፍ ያለው ፖሊስና ወታደር ነው የሚኖርባት - ሳዑዲ! ሌላ ቃል ብትተነፍስማ የሐሙሱ ጎራዴ ነው ተስሎ የሚጠብቃት፡፡ በውኃ ቀጠነ ሰዎች በሚታረዱባት ሀገር አራጆች ከሕግ በላይ እንደሆኑም ይነገራል፤ በዊስኪ መጠጥ ፍጆታ ሳዑዲ ከዓለም ስንተኛ ትሆን? አላውቅም ግን ከደረጃ ሰንጠረዥ እንደማትወጣ እገምታለሁ - ዋናው ነገር ቀን አይጉደልብህ ፡- ድሃ አትሁን፤ ወፍራም ሥልጣንም ይኑርህ፤ ያኔ ዓለም ያንተና የቢጤዎችህ ብቻ ትሆናለች፤ መገደልና መታሠር አንተ በምትጠላቸው ላይ እንጂ ወዳንተ አካባቢ ዝር አይሉም፤ ያሻህን ብትሠራ እንኳን! ብትገድል ሌላ ገዳይ ትሰይማለህ - እንዳስፈላጊነቱ የሚቀጣልህ ወይም የሚወቀስልህ፡፡ ብታጭበረብር ሌላ ምትክ ተጠያቂ ይኖርሃል - ያንተን አበሳ በሙሉም ሆነ በከፊል ወስዶ ዕዳህን የሚከፍልልህ - ሊያውስ ተጠያቂ ስትሆን አይደል? አንተ በቀን 24 ጊዜ የምታደርገው ተራ ነገር ድሃው በአሥር ዓመት አንዴ ቢያደርግ እሱ ወንጀለኛ ነውና ይገደላል ወይ ይታሰራል፤ አንተ ግን ንጹሕ መልአክ ነህ፡፡ አየሃት የዚህችን ዓለም ነገር? ያልተማርክና በጭካኔህ የለየለት ዐውሬ ብትሆንም እንኳን ባለክብር ዶክትሬትና ሩህሩህ ባለራዕይ የሀገር አለኝታ ነህ፡፡ ባጭሩ ካለህ አለህ፤ ከሌለህ የለህም፡፡ ይህች ምድርና ነዋሪዎቿ እጅግ ያሳዝናሉ፡፡ የፊጥኝ ታስረው የተያዙት በማን እንደሆነ ስንገምተውና ስንረዳው ደግሞ ይበልጥ ስፍስፍ ልንልላቸው እንገደዳለን፤ ሁላችን በአንድ ወይ በሌላ አስቀያሚ ሁኔታ የታሠርንባት የመከራና የሥቃይ ዓለም ናት፡፡ ማንኛችንም መረዳት ያለብን ነገር ኢትዮጵያ የሁሉም መሆኗን ነው፡፡ የሁሉ እንዳትሆን የሚሠሩ ካሉ ፈጣሪ ሤራቸውን ያክሽፍባቸው፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ በደምሳሳው የዋህና እንግዳ ተቀባይ ነው፤ ይህ ባሕርይው ግን ሊያስጠቃው አይገባም፡፡ በደካማ ጎኑ ገብተው ሊጎዱት የሚፈልጉ የውጭ ኃይሎች ይኖራሉና ፈጣሪ የሥራቸውን ይስጣቸው - ከውስጥ ተባባሪዎቻቸው ጭምር፡፡
ሃይማኖትን ማስፋፋት በራሱ መጥፎ አይደለም፡፡ ነገር ግን የምታስፋፋበት
መንገድ ነው ሊፈተሸና የአካሄድ እርምት ሊደረግለት የሚገባ፡፡ በራስ ሀገር ቤተ ክርስቲያን ቀርቶ በቤትህ ውስጥ ማምለክ እንዳትችል
እየተከለከልክና በሞት እየተቀጣህ በሰው ሀገር ገብተህ በሠይፍና በጎራዴ ሃይማኖትን ለማስፋፋት መሞከር ሰይጣናዊነት እንጂ የደግ
መንፈስ ውጤት ሊሆን አይችልም፡፡ በዓለም ብዙ ፍርደገምድልነት ይታያል፡፡ ብዙ ያናግራል፤ ግን ለአንድዬ እንተወው፡፡ ዛሬ ዛሬን
ይመስላል፡፡ ነገ ግን የተለዬ ይሆናል፡፡ ሁሉም እንደሥራው ማግኘቱ ቀድሞ የተነገረ ነውና ክፉም ለራስ ደግም ለራስ የሚለውን አንዘንጋ፡፡
ፈጣሪ ለኢትዮጵያ የሚበጀውን ያምጣልን፤ ሰላም፡፡
ዳግማዊ ጉዱ ካሣ