የህወሀት ባለስልጣናት በቡድን ተከፍለው ከፍተኛ ውጥረት ውስጥ ባሉበት በዚህ ግዜ ክልሉን በአስተዳደራዊ ስራ ሊመራ የሚችል ኃይል ባለመኖሩ የትግራይ ህዝብ ለከፋ ችግር መዳረጉን ሕዝቡ በይፋ ገለጸ፡፡
የሕወሀት ካድሬዎች መለስ ከሞተ በሁዋላ ለመጀመሪያ ግዜ በየወረዳው እየተዘዋወሩ የሕዝቡን ስሜት ለማጤን ባደረጉት ሙከራ እንደተረዱት ከሆነ ህወሀት ደክሞ እራሱን መምራት
ያልቻለ በመሆኑ ክልሉ ለከፋ አስተዳደራዊ በደሎች እየተዳረገ ነው ሲሉ ሕዝቡ መናገሩ ታውቆዋል፡፡
ዛሬ በትግራይ ክልል የወረዳና የቀበሌ አመራሮች የሚቆጣጠራቸው ጠፍቶ በህዝቡ ላይ
እንደልባቸው ከመጨፈራቸውም ባሻገር ያለ አንዳች ጥፋት ከደርግ ግዜ በባሰ ሁኔታ ሕዝቡን ያስራሉ …..ያሰቃያሉ….ይገድላሉ ሲሉ የክልሉ ነዋሪዎች በምሬት ሲናገሩ እንደነበር ከስፍራው የደረሰን ጥቆማ ገልጾዋል፡፡
ለፖለቲካ መጠቀሚያ ሲሉ የሀውዜን ከተማን በደርግ የጦር አውሮፕላን ሲያስደበድቡና ሕዝቡን ሲያስጨርሱ የነበረ ቢሆንም ዛሬም ያች ከተማ እንደወደመች እና አንዳችም የመሰረተ ልማት እንቅስቃሴ ያልተደረገባት ከመሆኑም በተጨማሪ ሕዝቡ የልማት ጥያቄ በማንሳቱ ሴት ወንድ…. ወጣት ሽማግሌ ሳይሉ እያሰሩ እየገደሉዋቸው እንደሆነና ከደርግ ጅምላ ጭፍጨፋ ያልተናነሰ በደል እየተፈጸመባቸው መሆኑን ነዋሪዎቹ እየገለጹ ይገኛሉ፡፡
የመለስን ራዕይ እናስፈጽማለን እያሉ እየዳከሩ የሚገኙትን የወያኔን የወረዳና የቀበሌ መሪዎች የትግራይ ሕዝብ በቁጣ አሳፍሮ የመለሳቸው ሲሆን በተለይ የሽሬ እና የሁመራ አውራጃ ነዋሪዎች መለስ በሕይወት እያለም አንዳችም የረባ መሰረተ ልማቶች እንዲከናወኑ ሳያደርግ አሁን ከሞተ በሁዋላ በሙት መንፈስ ራዕዩን እናስፈጽማለን ማለታችሁ አስገራሚ ብቻ ሳይሆን ከሞተው ግለሰብ ጋር ሀሳባችሁ አብሮ የተቀበረ በመሆኑ በእኛ ዘንድ ተቀባይነት አይኖረውም ብሎ አሳፍሮ እንደመለሳቸው ከስፍራው የደረሰን ጥቆማ ገልጾዋል፡፡
ወትሮም ሀገራዊ አጀንዳ ያልነበረው…..የሀገሪቱን ሕዝቦች ለአገዛዙ እንዲመቸው በጎጥ እና በመንደር እየከፋፈለ ሲያምሰን እንዳልነበር…የትግራይን ሕዝብ ከተቀረው የሀገሪቱ ሕዝቦች ለያይቶ ዳግም እንዳንገናኝ እንዳላደረገ ዛሬ በመለስ ራዕይ የተጀመሩትን እናስፈጽማለን መባሉ የማይሆንና የማይዋጥልን ነው ሲሉም መናገራቸውን ከስፍራው የደረሰን ጥቆማ አስረድቶዋል፡፡
የትግራይ ሕዝብ ከሌሎች ኢትዮጵያዊ ወገኖቹ እንዳይገናኝ እና ጨርሶ እንዲለያይ ያላሰለሰ ጥረት ስታደርጉ ነበር ያለው ሕዝቡ ለሰራችሁት ስህተት እና ጥፋት በይፋ ይቅርታ ካልጠየቃችሁ አሁንም ሆነ ወደፊት ከናንተ ጋር አብረን አንጉዋዝም በማለት ሕዝቡ ለ‹ድሬዎቹ አስደንጋጭ ማስጠንቀቂያ መስጠቱ ታውቆዋል፡፡
በሕዝቡ ሀሳብ ተስማምተው የተመለሱ የወረዳ ካድሬዎች በቀጥታ ለክልሉ ከፍተኛ ባለስልጣናት የህዝቡን ጥያቄ ያቀረቡ ቢሆንም ሕዝቡን ያሳመጻችሁ እናንተ ናችሁ በሚል ከስልጣናቸው መባረራቸውን ከስፍራው የደረሰን ጥቆማ አብራርቶዋል፡፡
መቀሌ የሚገኘው በአባይ ወልዱ የሚመራው አንዱ የወያኔ ክንፍ ካድሬዎቹን ወደ ተለያዩ ወረዳዎች እና ቀበሌዎች ልኮ የህዝቡን የልብ ትርታ አድምጠው እንዲመለሱ የላካቸው ቢሆንም ይዘው በመጡት መልስ በመደናገጥ ከአዲስ አበባው ቡድን ጋር ወግናችሁዋል በሚል ከስልጣናቸው ያባረታቸው መሆኑን ከመቀሌ የደረሰን ጥቆማ አስረድቶዋል፡፡
ከፍተኞቹ የህወሀት ባለስልጣናት እርስ በርስ መተማመን ተስኖዋቸው አንዱ አንዱን በጥርጣሬ እያየ ባለበት በዚህ ግዜም ባለፈው ሳምንት በመቀሌ በተደረገው የማዕከላዊ ኮሚቴ አባሎች ስብሰባ ላይ ንትርክ እና ጭቅጭቅ የነበረ ሲሆን በቅርቡም የተለያዩ ሹም ሽሮች ይደረጋሉ ተብሎ እየተጠበቀ ይገኛል፡፡
በአሁኑ ሰዓት የመቀሌው በአባይ ወልዱ የሚመራው ቡድን የትግራይ ክልል መንግስታዊ መዋቅሩን ተጠቅሞ የአዲስ አበባውን ቡድን ከህዝቡ ለማራቅ ሙከራ እያደረገ ሲሆን በአንጻሩ በደብረጽዮን የሚመራው ይመራል እየተባለ የሚነገርለት የአዲስ አበባው ቡድን ደግሞ በሙስና ሰበብ እያሰረና ከስልጣናቸው እያነሳ በመገኘቱ በህወሀት ውስጥ የተፈጠረው ሽኩቻ እየሰፋና እየገዘፈ መምጣቱ እየተነገረ ይገኛል፡፡
በቅርቡም በመቀሌ ከተማ በተደረገው የማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ የእነ አባይ ወልዱ ቡድን በእነ ደብረጽዮን ላይ የበላይነቱን ለመያዝ ሲል አዲስ አደረጀጃጀት እና አዳዲስ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባሎችን ለማምጣት በስውር ሰፊ ስራ እየሰራ እንደሚገኝም ተጠቁሞዋል፡፡
የእነ ደብረጽዮን ቡድን ደግሞ ለሀገር ሳይሆን ለስልጣን ….ለሕዝብ ሳይሆን ለግለሰቦች በማሰብ እና ያኛውን ለማዳከም የሙስና ምንጠራ እያደረጉ ሲሆን የህወሀት ቁልፍ ሰው ከተባለለት የገቢዎች እና ጉምሩክ ባለስልጣኑ ገብረዋህድ ቀጥሎ የደህንነት ምክትል ኃላፊ የሆነውን ግለሰብ ጭምር ዘብጥያ በማውረዳቸው ትንቅንቁ እንደቀጠለ፤ አመላ‹ች ሆኖዋል፡፡
መለስ በሕይወት እያለ የሚስቱን ገመና ለመሸፈን ሲል በሙስና እስከ አንገታቸው ድረስ የተዘፈቁ ቁጥራቸው የበዙ የወያኔ ባለስልጣኖች መኖራቸውን እያወቀ ስልጣኔን ካልተጋፉ ምን ቸገረኝ በሚል ስሜት የነበረ ቢሆንም እሱ ከሞተ በሁዋላና አሁን በህወሀት መሀከል በተፈጠረ ትርምስ ምክንያት በተጀመረው የሙስና ምንጣሮ ከፍተኛ ፈላጭ ቆራጭ የሆኑ ግለሰቦች ዘብጥያ የወረዱ ሲሆን ከነዚህ ግለሰቦች ጋር በሽርክና ስትሰራ የነበረችውና በቢሊዮን የሚቆጠር የሀገር ሀብት ያሸሸችው አዜብ መስፍን ጉዳይም ለግዜው በሚል በእንጥልጥል የቆየ ይሁን እንጂ የደብረጽዮን ቡድን ከተጠናከረ ሴትዮዋም ዘብጥያ መውረድዋ አይቀሬ እንደሆነ በስፋት እየተነገረ ይገኛል፡፡
ለዚህም ማሳያ ከኤፈርት ዋና ስራ አስኪያጅነት ተነስታ ከሌሎችም ወሳኝ ቦታዎች ተገድባ የመለስ ፋውንዴሽን ላይ ብቻ ተመድባ እንድትሰራ መደረጉ ወደፊት የነደብረጽዮን አቁዋም እየጠነከረ ከመጣ ያለ ማወላወል ከጉዋደኞችዋ ጋር እስር ቤት ልትቀላቀል ትችላለች ተብሎዋል፡፡
የወያኔ
ቡድን ባለስልጣናት የውስጥ ችግሮቻቸውን መፍታት ተስኖዋቸው እርስ በርስ የጎሪጥ እየተያዩ ባሉበትና ሙስለሙ ሕብረተሰብ ያነሳውን
የፍትሕ ጥያቄ ለመመለስም ሆነ ውጥረቱን ለማርገብ ባልቻሉበት በዚህ ግዜ በክርስቲያኑ ሕዝብ ላይ ያነጣጠረ የጥላቻ ቅስቀሳ መጀመራቸው
ታወቀ፡፡
በስብሀት
ነጋ አይዞህ ባይነት በፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር ሽፈራው ተክለማርያም ጥናታዊ ጽሁፍ አቅራቢነት በአፍሪካ ሕብረት መሰብሰቢያ አዳራሽ
በተደረገው ስብሰባ ላይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ ወንጀል እንደሚፈጸምና አክራሪዎችም እንዳሉ በመግለፅ
በይፋ መናገሩ ታውቆዋል፡፡
መያዣ
መጨበጫው የጠፋባቸው የወያኔ ባለስልጣናት የሙስሊሙን ሕዝብ ጥያቄ ከሽብርተኝነት ጋር በማያያዝ የጥላቻ ዘመቻ ቢከፍቱም አልሳካ ሲላቸው
በቅርቡ ደግሞ በክርስትና እምነት ተከታዮች ላይ እጅግ አስፈሪ የሆነ ቅስቀሳ መጀመራቸው ታውቆዋል፡፡
ስብሀት
ነጋ ሰሞኑን በስብሰባው ላይ እና በተለያዩ የወያኔ ሚዲያዎች ላይ እንዳንጸባረቀው ከሆነ የክርስትና እምነት ተከታዮችም ጀርባቸው
ሊጠና እና ክትትል ሊደረግባቸው ይገባል ብሎ በመናገሩ በሕዝበ ክርስቲያኑ ዘንድ ቁጣን መቀስቀሱ ታውቆዋል፡፡
እንደፈለገውና
ያሻውን እየተናገረ የሚዘላብደው ይሄው የወያኔ ባለስልጣን ስብሀት ነጋ በሙስሊሙ ህብረተሰብ ብቻ ሳይሆን በኦርቶዶክስም ውስጥ አክራሪ
እና ጽንፈኞች ስላሉ ጉዳዩን በጥልቀት ተከታትለን ልንመረምረው ይገባል በማለት በኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ላይ ጣቱን መቀሰሩም
ታውቆዋል፡፡
የውስጥ
ችግሮቻቸውን ለመፍታት ያልቻሉት የወያኔ ቡድን ከፍተኛ ባለስልጣናት የራሳቸውን የውስጥ ችግር ለመሸፋፈን ሲሉ ሰላማዊ ጥያቄ ያቀረበውን
የሙስሊሙን ህብረተሰብ ሽብርተኛ የሚል ተቀፅላ ሰጥተው አንገቱን እንዲደፋ ለማድረግ ቢሞክሩም አልሳካ ሲላቸው አሁን ደግሞ ፊታቸውን
ወደ ክርስትና እምነት ተከታዮች ማዞራቸው አሳፋሪና አሳዛኝ ከመሆኑም ተጨማሪ የሀገርና የህዝብ ከፋፋይ ሴራ ነው ሲሉ የእምነቱ ተከታይ ምሁራኖች
በንዴት ይገልጻሉ፡፡
የወያኔ
ከተማ አፈራሽ ባለስልጣኑ የደኢህዴኑ ሽፈራው ተክለማርያም አቀረበ በተባለው ጥናታዊ ጽሁፉ ላይ በሀገራችን በሁሉም ሀይማኖቶች በተለይ
በኦርቶዶክስ እምነት ሽፋን…በእስልምና እምነት ሽፋን….በፕሮቴስታንት እምነት ሽፋን አክራሪነትንና ፅንፈኝነት አስተሳሰብ ብቻ ሳይሆን
ተግባራዊ እንቅስቃሴ አራማጆች የተከማቹበት በመሆኑን አፋጣኝ እርምጃ ሊወሰድ ይገባል በማለት የወያኔን አቁዋም መግለጹን ተከትሎ
ሕዝቡ በሰላም አንገቱን ደፍቶ በመኖሩ ፍርሀት ስላደረባቸው ብቻ ሊያምሱት ከላይ እታች ማለታቸው አስገራሚ ነው ተብሎዋል፡፡
የህዝበ
ክርስቲያኑ ዝምታ ያስደነገጠው የወያኔ ቡድን ከውስጥ ችግሮቹ ጋር ተዳምሮ አላስቀምጥ ስላለው ብቻ በተለያዩ ምክንያቶች ሕዝቡን ስብሰባ
እየጠራ የክርስትና እምነት ተከታይ አክራሪዎች ስለተፈጠሩ ልትጠነቀቁ ይገባል እያለ ምንም ባልተፈጠረበት እና ሰላማዊ በሆነችው ቤተ
ክርስቲያን ውስጥ ውዥንብር መፍጠሩ አስገራሚና አሳፋሪ እጅግ አደገኛ በመርዝ የተለወሰ ፕሮፓጋንዳ መሆኑን ሕዝቡ ሊረዳ ይገባል ሲሉም
የእምነቱ ተከታይ ምሁራኖች ተናግረዋል፡፡
ተስፋ
የቆረጠው እድሜ ጠገቡ ስብሀት ነጋ በበኩሉ በአሁኑ ሰዓት የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንን የፖለቲካ መጠቀሚያ ለማድረግ የሚፈልጉ ኃይሎች
እየተንቀሳቀሱባት በመሆኑ መንግስት አስፈላጊውን እርምጃ ሊወስድ ይገባል ሲል ማሳሰቢያ መስጠቱም ተደምጦዋል፡፡
ስብሀት
ነጋና የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትር ሽፈራው ተክለማርያም በሰጡት ማስጠንቀቂያ ላይ የማሕበረ ቅዱሳን አባላት ጽንፈኛና አክራሪዎች በመሆናቸው
ክትትል ሊደረግባቸው ይገባልም ብለዋል፡፡
የወያኔ
አቀንቃኝ የነበሩት አባ ጳውሎስ ከሞቱ በሁዋላና አቡነ ማትያስ ከተተኩ ወዲህ በቤተክህነት ውስጥ ከላይ እስከ ታች ድረስ በብሔር
ተመድበው ያለ እውቀታቸው የተቀመጡ እንዲነሱ በመደረጉ እንዲሁም በአዲስ አበባ በሚገኙ ርዕሰ አድባራት ውስጥ ቤተክርስቲያንን ሲያምሱ….
ሕዝበ ክርስቲያኑን ሲጫወቱበት የነበሩ ከወያኔ ጋር ቅርብ ግንኙነት ያላቸው ካድሬ ካሕናት በመመንጠራቸው ስጋት የገባቸው የወያኔ
ቱባ ባለስልጣናት የተባረሩትን ለመመለስ በማሰብ ሕዝበ ክርስቲያኑን አክራሪ እና ሽብርተኛ እያሉ ተለጣፊ ስም እየሰጡ እያስፈራሩ
ይገኛሉ፡፡
አዲሱ
ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ገና በተሾሙ ጥቂት ቀናት ውስጥ ሲኖዶሱን ሰብስበው በቤተክህነትም ሆነ በቤተክርስቲያን ውስጥ ያለ እውቀትና
ችሎታቸው ተመድበው የተቀመጡ ግለሰቦች እንዲነሱና ሌሎች እውቀት ያላቸው በቦታው እንዲቀመጡ በማድረጋቸው የተደናገጡት የወያኔ አቀንቃኝ
እና ተላላኪ ካህናቶች ከወያኔ ባለስልጣናት ጋር በመሆን የተጀመረውን ምንጠራ ለማስቆም አሸባሪና ጽንፈኛ እያሉ ቢያስፈራሩም አሁንም
ድልድሉና ምንጠራው እንደቀጠለ ከቤተክህነት የደረሰን ጥቆማ ገልጾዋል፡፡