አውደ ታሪከ
ኢመማና የካቲት፣ የማህበሩ ውጣውረድ በጨረፍታ።
ዘመን በመቁጠር ሂደት የወርና የሁኔታ ግጥምጥሞሽ ይከሰታል። በሰነድ የተያዘ ማስረጃ እንደሚያሳየው የካቲት 14 ቀን 1941ዓ.ም “የመምህራን ኅብረት” በደግማዊ ምንልክ ት/ቤት በአዲስ አበባ ተቋቋመ። የወቅቱ የኅብረቱ ሊቀመንበርም አቶ ሚሊዮን ነቅነቅ ነበሩ። ይህ የመምህራን ኅብረት ስያሜውን እንደያዛ እስከ 1954 ዓ.ም ድረስ ቀጥሏል። ኅብረቱ ከየትኛውም አካል መንግሥትን ጨምሮ አደናቃፊ ኃይል ሳይገጥመው እንዲያውም ድጋፍ እየተደረገለት ነበር እዚህ ወቅት ድረስ የቀየው። ምዝገባ ፣ በሕግ የመታወቅና ያለመታወቅ ጥያቄም አልተነሳም ነበር። ኅብረቱ በ1953 ዓ.ም የዕውቅናና የምዝገባ ጥያቄ ተነስቶ በዚያውም አፈናና የመንግሥት ጣልቃገብነት ተጨምሮበት ጉዞው አስቸጋሪ ሆነ።
ከላይ የተጠቀሰው ሁኔታ እንዳለ ሆኖ 12ኛው በፈረንሳይ አገር ተደርጎ የነበረው የዓለም መምህራን ማህበር ጉባኤ 13ኛው ጉባኤ በአፍሪካ ውስጥ እንዲደረግ ወስኖ ስለነበር በወቅቱ የትምህርት ሚኒስትር ውስጥ ከፍተኛ ሥልጣን የነበራቸውና ቀደም ብሎም መምህርና በመምህራን ማህበር አመራር ላይ የነበሩት አቶ መኮንን ዶሪ ትምህርት ሚኒስትርን በመወከል 13ኛው የዓለም መምህራን ማህበር ጉባኤ በ1957 ዓ.ም በኢትዮጵያ እንዲካሄድ ጋበዙ። ነገር ግን ማህበሩ በአገር አቀፍ ደረጃ ባለመቋቋሙና ሕጋዊ ሰውነት የሌለው መሆኑ አወዛጋቢ ሆነ። ወዲያውኑ ጉዳዩ ለንጉሡ ቀርቦና ፈቅደው የመምህራን ኅብረት ከ1953 ዓ.ም ጀምሮ አቅርቦት የነበረው የምዝገባና ሕጋዊነት ጥያቄ በመጋቢት 14 ቀን 1957 ዓ.ም ሕጋዊ ሰውነት አግኝቶ “ኢመማ “ በሚል ስያሜ ተመዘገበ። ንጉሡ ይህ ድርጊት የፈጸሙት የዓለም አቀፍ ዝናን ለመግኘት ሲሉና የዓለም መምህራን ማህበርም የአሜሪካን መንግሥት ድጋፍ ስለነበረው መጋፋቱን ባለመፈለግ እንደሆነ ይነገራል። ከዚያም በየጠቅላይ ግዛቶቹ የማህበሩ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች ተቋቁመው ወኪሎቻቸውን መላክ በመቻላቸው 35 አባላት ነሐሴ ወር 1957 ዓ.ም በአፍሪካ አዳራሽ በተካሄደው 13ኛ የዓለም መምህራን ማህበር ጉባኤ ላይ ተሳታፉ። ከእነዚህ ተሳታፊዎች ዶ/ር ጥቀሄር ኃይሉ ፣ አቶ ይልማ ወርቅነህ ፣ አቶ ኪሮስ ሐብቱና አቶ ደምሴ በላይ ዋና ተውካዮች ነበሩ። ይህ የመምህራን የትግልና የመስዋእትነት ውጤት መሆኑን ሲያመለክት ከ1953- 1957 በነበረው ጊዜ በአገር ውስጥና በውጪ የኢመማ ግንኙነት ተዳክሞ የመታየቱ ሰበብ በ1953ቱ የመፈንቅለ መንሥሥት ማህበሩ ድጋፍ ሰጥቷል የሚል እንደነበረ ይታወቃል። ከዚሁ ጋር ተያይዞም በ1958 ዓ.ም ላይ የወጣው የመምህራን የደመወዝ እስኬል በመምህራን በኩል ተቀባይነት በማጣቱ በ1960 ዓ.ም በአቶ ከበደ ደስታ ይመራ የነበረው የአዲሰ አበባ መምህራን ማህበር መምህራንን አስተባብሮ መንግሥት ያልጠበቀው የሥራ ማቆም አድማ ማድረጋቸው ሌላ የመንግሥት ጣልቃገብነት ፣ የአፈናና እንዳሁኑ የከፋ ባይሆንም የመከፋፈል እርምጃ መከሰቱ አልቀረም። ቀደም ሲል በመምህራን የቀረቡት የደመወዝ እስኬል ጥያቄዎች ምላሽ ሳያገኙ የትምህርት ዘርፍ ክለሳ (Education Sector Review) ወጥቶ ይፋ ሆነ። ይህም የትምህርት ዘርፍ ክለሳ በሚከተሉት ነጥቦች ላይ የተመሰረቱ ተቃውሞ ገጠመው፡-
·
የሴክተር ሪቪው ተግባራዊነትና ውጤቱ ለመምህራን ሳይገለጽ በሚስጢር መያዙ፣
·
መምህራን ፣ ወላጆችና ተማሪዎች ተሳትፈው አስተያየት ያልሰጡበት መሆኑ፣
·
በሙከራ ሳይታይ በአገሪቱ በሙሉ በሥራ ለማዋል መሞከሩ፣
·
ለከፍተኛ ትምህርት ገንዘብ እንዲከፈልበት መጠየቁ፣
·
ለመምህራን የታሰበው መነሻ ደመወዝ ብር 153 መሆኑ
·
በገጠር የመሬት ይዞታ ለውጥ ሳይደረግበት የገበሬውን ኑሮ ያሻሽላል መባሉና ሌሎች
በዚህም መሰረት በ1966 ዓ.ም ከታሕሣሥ 12 እስከ 15 የዘለቀ ልዩ ጠቅላላ የማህበሩ ጉባኤ ተጠርቶ የሴክተር ሪቪውና የመምህራን ደመውዝ እስኬል መጠን ወስኖ ከሌሎች ተዛማጅ ጥያቄዎች ጋር መልስ እንዲሰጣቸው ተስማምቶና ወስኖ ተነሳ። እስከ የካቲት 11 ቀን 1966 ዓ.ም ድረስ ለጥያቄዎቹ መልስ ሳይሰጥና የመምህራን ድምፅ በወኪሎቻቸው አማካይነት ቀርቦ ሳይሰማ ቢቀር ማህበሩ ሁኔታው እንዲቃና የተቻለውን ሁሉ ስለፈጸመ የመሰላቸውን እርምጃ ቢወስዱ በኃላፊነት እንደማይጠየቅም አሳወቀ። የመምህራን ጥያቄ መሰረታዊና ሥር የሰደደ መሆኑን ያልተገነዘበው ትምህርት ሚኒስቴር ግን በራሱ አካሄድ የወሰነውን ፕሮግራሙን ተግባራዊ ማድረግ ስለጀመረ አፈጻጸሙ ማህበሩንም ሆነ ምህራንን ይበልጡን ለተቃውሞ አነሳሳ። ዘግይቶም ቢሆን ትምህርት ሚኒስቴር ፣ የሠራተኛ ማስተዳደሪያ ኮሚሽንና የኢመማ መሪዎች በአንድነት ለድርድር በያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት ሰብሰባ ቢያደርጉም ስምምነት ላይ አልተደረሰም። ጉዳዩን ስንመለከተው የዘውዱ ሥርዓት ባለሥልጣናት በውይይትና በመደራደር ረገድ ከደርግና ከወያኔ ተሿሚዎች በተሻለ ደረጃ መሆናቸውን ነው። ከላይ ለማስታወስ እንደሞከርነው የማህበሩ የታሕሣሥ 1966 ልዩ ጠቅላላ ጉባኤ ባሳወቀውና በማስጠንቀቂያው መሠረት የካቲት 11 ቀን 1966 ዓ.ም መምህራን በመላው አገሪቱ የሥራ ማቆም አድማ መቱ። ታክሲ ነጂዎች በአዲሰ አበባ የካቲት 13 ቀን 1966 ዓ.ም ሥራ በማቆም ከመምህራን ጎን ቆሙ፤ ሥራ ባላቆሙት ታክሲ ነጂዎች ላይም እርምጃ ወሰዱ። የሠራተኛ ማህበራት አባላትም ሥራ ለማቆም ማቀዳቸው ታወቀ። ይህ ሥርዓት ለውጥ አማጭ የኢትዮጵያ አብዮት ዋዜማ መሆኑ ለኢመማ የሕዝብ አለኝታነት አሌ የማይባል ነው። መምህራን ሥራ ማቆማቸውን ሲሰሙ ንጉሡ፡-
·
አስፈላጊ ሁኔታዎች እስኪሟሉ ሴክተር ሪቪው ለሌላ ጊዜ እንዲተላለፍ፣
·
የደመወዝ ጉዳይ ተጠንቶ በአጭር ጊዜ ውስጥ ውሳኔ ስለሚደረግ መምህራን ይህን አውቀው ሥራ እንዲጀምሩ የካቲት 16 ቀን 1966 ዓ.ም አስታወቁ። በዚህም ተባለ በዚያ የጥያቄው ዓይነትና ብዛት አገር አቀፍና ሕዝባዊ ይዛት ተላብሶ ሕዝባዊ አመጽ( አብዮት) አስነስቶ የዘውዱን ሥርዓት አስወገደ። በወቅቱ የኢትዮጵያ ህዝብ የጋራ ጥያቄዎች ከነበሩት ጥቂቶቹና ጎላ ብለው ይታዩ የነበሩት የሚከተሉት ናቸው፡-“ መሬት ላራሹ” ፣ “ የድሃ ልጅ ይማር “ ፣ “ ዲሞክራሲያዊ መብቶች ያለገደብ ይከበሩ “ ፣ “ የመምህራን የደመወዝ እስኬል ይሻሻል” ፣ “ በጋዝ ላይ የተደረገው ጭማሪ ይነሳ” ፣ “ የሃይማኖት እኩልነት ይከበር ” ፣ “ ሕዝባዊ መንግሥት ይቋቋም “ ፣ “ የሴቶች ድርብ ጭቆና ይወገድ “ ፣ “ የሴቶች የእኩልነት መብት ይከበር “ ፣ “ፊውዳልዝም ይውደም “ ፣ “ ኢምፔሪያሊዝም ይውደም “ ፣ “ የሠራተኞች የሥራ ሰዓት በቀን 8 ሰዓት ይሁን “ ፣ “ የብሔረሰቦች የእኩልነት መብት ይከበር “ --- ወዘተ።
ኢመማ በአብዮቱ ወቅት የተጫወተው ሚና በዋዛ የሚታይ አልነበረም። አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ልጅ እንዳልካቸው መኮንን ውጥረቱን ለማስታገስ የኢመማ አመራር አባላትን ጠቅላይ ፖስታ ቤት ቢሮአቸው አስጠርተው መምህራንን እንዲያስታግሱላቸው ትብብር ጠይቀው እንደነበር ይታወሳል። የጦር ኃይሎች ፣ የፖሊስ ሠራዊትና የብሔራዊ ጦር ሰኔ 21 ቀን 1966 ዓ.ም እንደተቋቋመ አንድ ቡድን ኢመማ ጽ/ቤት መጥቶ አነጋግሯል፤ የትብብር ጥያቄም አቅርቧል። ሐምሌ 3 ቀን 1966 ዓ.ም ኮሚቴው ለኢመማ በጻፈው ደብዳቤ መነሻነት ከሐምሌ 3-5 ቀን 1966 ዓ.ም የተሰበሰበው የኢመማ ሥራ አስኪያጅ ኮሚቴ በሰጠው መልስ ላይ “ ኮሚቴ “ የሚለውን “ደርግ “ በሚል ስለተካው ወታደራዊ ኮሚቴው ከኢመማ በወሰደው “ ደርግ “ ብሎ እራሱን እንደሰየመ ይታወሳል።
የኢመማ ሥ/አ/ኮሚቴ ለአገሪቱ ጠቃሚ ነው ብሎ ያመነበትን የመፍትሔ ሐሳብ በ4 ገጽ ጽፎ ለደርግ አቅርቦ ነበር። ሕዝቡ ምን ዓይነት መንግሥት ቢቋቋም እንደሚፈልግ እንዲጠየቅ ፣ ሌላ ሕገ መንግሥት ከየክፍሎቹ በሚወከሉ ጠበብት እንዲዘጋጅ ፣ እስከዚያው ድረስ ደርግ ከሕዝባዊ ማህበራትና ከመሳሰሉት ጋር በመካከርና በመደጋገፍ መሠረታዊ የሐሳብ መግለጽ ነፃነትና ሰብአዊ መብቶች ተጠብቀው ለተወሰነ ጊዜ አገሪቱ በጊዜያዊ ሕገ መንግሥትና አዋጆች እንዲትተዳደር ያለውን ሐሳብና ድጋፍ ገልጾ ነበር፤ በሂደቱም የራሱን ርቱዕ አስተዋጽኦ አድርጓል። ውሎ አድሮ ግን የወታደራዊ ቡድን (ደርግ ) ክንዱን እያፈረጠመ በጠመንጃ የመግዛት አባዜ እየተጠናወተው በመምጣቱ ኢመማና ደርግ ዓይንና ናጫ ሆኑ። በተለይ ጳጉሜ 1967ዓ.ም በጅማ የማህበሩ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ የሥርዓተ ትምህርት ዝግጅትና ከዚሁ ጋር አስታኮ የወታደራዊውን መንግሥት አካሄድ በመቃወም የኢኮኖሚና የመብት ጥያቄዎችን አቅርቦ መልስ የማይሰጥ ከሆነ ሕዳር 7 ቀን 1968 ዓ.ም መምህራን የሥራ ማቆም አድማ እንደሚያደርጉ ወስኖ ተበተነ። አድማውም አልተሳካም ፣ ስብሰባም አልተቻለም ፤ ምክንያቱም ደርግ ለጥያቄዎቹ መልስ ለመስጠት በመወያየትና በመደራደር ፋንታ የኃይል እርምጃና አፈናን በመምረጡ ነበር። ከዚሁ ጋር ተያይዞ የኢመማ መሪዎች ታደኑ ፣ ታሠሩ ፣ ተገደሉ ፣ ተሰወሩ ፣ ለሰደት ተዳረጉ ። እስከ1971ዓ.ም ድረስ ዋናው ማህበር ሥራ በማቋረጡ የኢመማ ጽ/ቤት ሠራተኞች እንኳ ደመወዝ የሚከፈላቸው አጥተው በብድር ስም የወሎ መምህራን ማህበር እየከፈላቸው እንደቆየ የማህበሩ ታሪክ ያስረዳል።ከዚያ በኋላ አፋኙ ደርግ አንድ ጊዜ በኢማሌድኅ ( የኢትዮጵያ ማርክሳዊ ሌንናዊ ድርጅቶች ኅብረት)፣ አንዴ በኢሠፓአኮ( የኢትዮጵያ ሠራተኞች ፓርቲ አደራጅ ኮሚሽን)፣ በሌላ ጊዜ በኢሠፓ ( የኢትዮጵያ ሠራተኞች ፓርቲ) አመራር ሥር እያለ ማህበሩን ምርኮኛ አባላቱን ጥገት አድርጎ እስከ 1983 ዓ.ም ድረስ ባተ።
በ1983 ዓም በውስጥ ቦርቧሪዎች ቅጥረኝነትና በውጪ ጠላቶቻችን አስተባባሪነት ወያኔ/ኢህአዴግ የአገሪቱን ጦር በሻጥር አተራምሶ፣ ደርግ አገሪቱ ያፈራቻቸውን እውቅ የጦር ጄኔራሎች ማጥፋቱን ተጠቅሞ አገሪቱን በመላ ከተቆጣጠረ በኋላ የሕዝባዊ ማህበራትን እያፈረሰ ፣ ንብረታቸውን እየወረሰና ጽ/ቤቶቻቸውን ሲዘጋ ምክንያቱ በውል ባልታወቀ ሁኔታ በኢመማ ላይ ተመሳሳይ እርምጃ አልወሰደም ። ይሁን እንጂ የማህበሩን አመራር ይዘው የቆዩት መሪዎች አዲሱ ክስተት ውስጥ በነፃነት መሥራት የማይችሉ መሆናቸው ስለገባቸውና የማህበሩ ቆይታም በኢሠፓ ቅኝት የታጠረ ስለነበር ፣ ከመምህራንም ተቃውሞ ስለገጠማቸው ሌላ ምርጫ ተካሄዶ ለአዲስ መሪዎች አስረክበው ለመውጣት በመንግሥት ስም የተቀመጠውን ቡድን ጠይቀው ተፈቀደላቸው። ወቅቱ ዝብርቅርቅ ሁኔታ የተፈጠሩበት ስለነበር በመላው ኢትዮጵያ ምርጫ እንዲካሄድ የሚያደርግ አካል ባለመኖሩ በትምህርት ሚኒስቴር አስተባባሪነት ማህበሩን እንደገና የሚያደራጅና ጉባኤ ጠርቶ ምርጫ የሚያካሄድ አስተባባሪ ኮሚቴ እንዲቋቋም ሁኔታዎች ተመቻችተው ሰኔ 21 ቀን 1984ዓ.ም ልዩ የምክር ቤት ስብሰባ ኮሚቴው ተመረጠ። መምህራን በተወካዮቻቸው በኩል አዲስ ለተቋቋመው የአስተባባሪ ኮሚቴው የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ በርካታ ጥያቄዎችን ልከው ኮሚቴው ከተላኩት ሁሉ ጨምቆ 20 ጥያቄዎችን ለሽግግር መንግሥቱ አቀረበ ። “ድመት መንኩሳ አመሏን አትረሳ “ እንዲሉ ነውና ወያኔ/ኢህአዴግ የአውሬነት ተፈጥሮው አይሎ ወጣና በጥፍሩ መቧጠጥ ፣ በጡጫውም መርገጥ ፣ ፍትሕንም መደፍጠጥ ገና በጥዋቱ በሥልጣን ማሟሻው ጀመረ። በተለይ “ ኢትዮጵያ “ የሚል ስም ለመስማትም ሆነ ለመናገር ይጠየፍ ስለነበር ማህበሩን በዘር ፖለቲካው ትይዩ “ የአማራ” ፣ “ የኦሮሞ “ ፣ “ የትግራይ “ ፣ “ የሱማሊያ” ፣ “ የደቡብ “ ---- ወዘተ መምህራን ማህበር እያለ ለማዋቀር የቀየሰውን እቅድ አዲሱ የኢመማ አመራር በግልጽና በአደባባይ ስለተቃወመ ወያኔ/ኢህአዴግ በማህበሩና በአባላቱ ላይ እመቃ፣ ወከባ ፣ እስራት ፣ ማፈናቀል ፣ መሰወር ፣ በአውራ ጠራራ መግደል ( የአቶ አስፋ ማሩን ግድያ ያስታውሷል) ሥራየ ብሎ ተያያዘው። ሁለንተናዊ ድጋፍ በመስጠት ተለጣፊ ማህበር አቋቁሞ ሕጋዊ ማህበሩንና አመራሩን እየከሰሰ 4 ጊዜ ለኢመማ ፍ/ቤት ቢፈርድም በአስፈጻሚው አካል ፍትህ እንዲኮላሽ አድርጓል።የባሰውና የከፋው አደጋ የትምህርቱ ጥራት እንዲዘቕጥ የሠራው በመምህራን ፣ በኢመማ ፣ በተተኪው ትውልድና በአገሪቱ ላይ ከደረሱት አደጋዎች የሚደመር ነው።ኢመማና መምህራን ካለፉት ሥርዓቶች በከፋ መልኩ አደጋ ላይ የወደቁት በዚህ ከፋፋይና አምባገነናዊ ቡድን ነው።
ዘንድሮ የካቲት ላይ ሆነን የየካቲት 1941 ዓ.ም የኢመማ ልደት ፣ በ1966 ዓም የካቲት የኢትዮጵያ መምህራን የመብት ጥያቄና ሕዝባዊ እንቅስቃሴ ፣ ከዚያም ቀጥሎ የሕዝብን ሥልጣን በጠመንጃ ነጥቀው እንቅጣህ ፣ እንግዛህ የሚሉትን ፋሽስቶች ስናስብ ላፍታ እንኳን ላለመታገል ዳተኛ የማንሆንበት የታሪክ አጋጣሚ ላይ እንዳለን ነው የሚሰማን። አሁንማ የአገራችን ህልውና በጥያቄ ምልክት ውስጥ የገባበት ሁኔታ ላይ ነው የምንገኘው ። ምን እስከሚሆን ነው ዝም ብለን የምንመለከተው? ቤታችን የውጪ ጠላቶቻችን ምሽግ ሆኖ የለ ! ክብር ፣ ነፃነት ፣ --- ሁሉም ነገር የሚገኘው በአገር ነው። ይህ ጉዳይ ለእኛ ለመምህራንና ለምሑራን ትልቅ አገራዊ ኃላፊነት ነው። ግዴታችንን እንወጣ ። ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ጀግኖች ጋር በመሆን ለአገራቸውና ለሕዝባቸው የሕይወት መስዋዕትነት የከፈሉት እና ዘርዓይ ደረስ ፣ ሞገስ አስገዶም ፣ አብርሃ ዶቦጭ እኮ መምህራን ነበሩ። ለአገር መሞት አኩሪ ግዳጅ መሆኑን ያስተማሩ ብርቅየ ጀግኖች ። አርአያነታቸውን ልንከተላቸው ይገባል። የካቲት ለኢትዮጵያ መምህራን ልዩ ትርጉም አለው ። ወያኔዎች ለባንዳነት ተልእኳቸውን ለማሳካት የተሰበሰቡበትን የካቲትን ሊያዜሙለት ሲዳዳቸው ስናይ ምንኛ በታሪክ ፣ በባሕል፣ በሕዝብና በእውነታ ላይ እየተቀለደ እንደሆነ በምሬት ነው የሚታወሰን።
የኢትዮጵያ መምህራን የካቲት ብዙ አባላት ፣ መሪዎች ፣ አጋሮቻቸው ሳይቀሩ ገድል የሠሩበት ስለሆነ ታሪኩን በተግባር እያደሱ ራሳቸውን ፣ ተተኪውን ትውልድ ፣ ባጠቃላይ አገሪቱን የሚታደጉበት እንዲሆን ትግሉን ከሕዝቡ ጋር በማቀናጀት እንዲገፉበት በሰደት የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር አባላት አስተባባሪ ኮሚቴ ጥሪውን በተደጋጋሚ ያቀርባል። እንኳን ለኢመማ 65ኛ ዓመት ምስረታ አደረሳችሁ ።
መምህራን የ1966ቱን የካቲት ታሪክ ይደግሙታል!!!
By Coordinating Commitee of Exiled Members of
Teachers Association
Email: eta1941@yahoo.com